የሻለቃ ዳዊት የዋሽንግተን ሲያትል ንግግር በሞረሽ ዕይታ!

የሻለቃ ዳዊት የዋሽንግተን ሲያትል ንግግር በሞረሽ ዕይታ!

የሻለቃ ዳዊት የዋሽንግተን ሲያትል ንግግር በሞረሽ ዕይታ!
To: Moresh Wegenie <mwaoipr@gmail.com>

ውድ ወገኖች

የተለመደውን ትብብራችሁ በመሻት ዛሬ ሃሙስ ሰኔ ፩ ቀን  ፳፱ ሺ ፱ ዓ.ም የወጣው መግለጫ መያያዙን እየገለጽን የሞረሽ ወገኔ ዐማራ ድርጅት የጀመረውን ረጅም ታሪካዊ የትውልድ ኃላፊነት እስከ ዘለቄታው በጽናትና በቆራጥነት ወደፊት በመግፋት ላይ የሚገኝ መሆኑንና ከመቼውም ጊዜ የበለጠ በዚህ የመጨረሻው መጀመሪያ በሆነው የዐማራ ሕዝብ እልህ አስጨራሽ የትግል ደረጃ ወቅት ከአንጡራ ና ጀግና የዐማራ ልጆች ብርቱ ሁለገብ ድጋፍ የምንጠብቅ መሆናችንንም በአንክሮ ና በትህትና እናሳስባለን።

ትግሉ ይቀጥላል!

ዐማራነት ወንጀል አይደለም።

አንድ ዐማራ ለሁሉም ዐማራ ፤ ሁሉም ዐማራ ለአንድ ዐማራ!

ሞረሽ ወገኔ ዐማራ ድርጅት

ማስታወቂያና ሕዝብ ግንኙነት መምሪያ

 

ሞረሽ ወገኔ የዐማራ ድርጅት            ሓሙስ ሰኔ ፩ ቀን  ፪ሺህ ፱ ..                         ቅፅ፭ ቁጥር  ፲፰

የሻለቃ ዳዊት የዋሽንግተን ሲያትል ንግግር በሞረሽ ዕይታ!

ሰዎች መልካም ሢሠሩና ሲናገሩ ማመስገን፣ መጥፎ ሢሠሩና ሲናገሩ ደግሞ መምከርና መገሰጥ ተገቢ ነው። ምንጊዜም ሁሉም ሰው ሕይዎቱን ሙሉ ስሕተት ብቻ እየሠራ አይኖርም። መልካም ነገሮችም ይሠራል። ልዩነት የሚኖረው የትኛው ሥራው ነው የሚያመዝነው? መልካሙ ወይስ መጥፎ የሚለውን መመዘኑ ላይ ነው። በዚህ ረገድ የሻለቃ ዳዊትን ሥራዎች መዝኖ፤ የማሞገሱም ሆነ የመውቀሱ ተግባር፣ እርሳቸውን የሚያውቁ፣ አብረዋቸው የሠሩ፣ የትምህርትና የሥራ ባልደረቦቻቸው ተግባር ይሆናል።

ሞረሽ ወገኔ ዐማራ ድርጅት ለዐማራ ነገድ ድምፅ ለመሆን የበኩሉን ድርሻ በመወጣት ላይ ያለ ድርጅት ነው። ስለዚህ ሻለቃውን በዚህ ንግግራቸው፣ ላለፉት 5 ዓመታት ሲጮኽባቸው የነበሩ አንኳር ጉዳዮችን እያነሱ፣ ዐማራውን ሲያወግዙ፣ በጠላትነት ፈርጀው የዘር ፍጅት በፈጸሙ ግለሰቦችና ስብስቦች ፊት በኩራት ቆመው በመናገራቸው ከልብ ልናመሰግናቸው እንወዳለን። ዳዊት ይህን የተናገሩት ከሞረሽ ሞገስና ምሥጋና ፈልገው አይደለም። ድርጊቱ ዕውነት ስለሆነ ብቻ ነው። በሌላም በኩል እርሳቸው «ኢትዮጵያዊ እንጂ፣ ዐማራ ሆኜ አስቤ አላውቅም» ቢሉንም፣ «ትንሽ ሥጋ እንደመርፌ ትወጋ»፣ « ምንም ብጠላው በወንድሜ ግንባር ደም አልይበት» የሚለው የአባቶቻችን አባባል አስሮ የያዛቸው ብቻ ሳይሆን፣ እንደ ሰብአዊ ፍጡር በዐማራው ላይ የተፈጸመው የዘር ፍጅት የሰው ልጅ ሊገምተው ከሚችለው በላይ በመሆኑ እንደ ሰው፣ እንደ አንድ ኢትዮጵያዊ ዜጋ አስበው የደረሱበት ድምዳሜ እንደሚሆን ይታመናል። በሌላ በኩል  ዘረኛው የትግሬ ወያኔ አገዛዝ ዓላማና በዐማራው ላይ እየፈጸመው ያለው የዘር ዕልቂት ማንም ሊሸፋፍነው ከሚችለው በላይ ሆኖ ገዝፎ የወጣ በመሆኑና ይህንንም ሕዝቡ በግልጽ በመቃወም እየተዋደቀለት በመሆኑ፣ አድበስብሰው ሊያልፉት ከማይችሉበት ደረጃ የደረሱ መሆኑን መገንዘባቸው እንደሆነ መረዳት ይቻላል።

ሻለቃ ዳዊት ወልደጊዮርጊስ ለአያሌ ዓመታት በዝምታ ወይም በይሉኝታ፣ ወይም በሌሎች ምክንያቶች አፍነው ይዘውት የኖሩትን ሐቅ፣ በዋሽንግተን ሲያትል «የአገራዊ ንቅናቄ» በጠራው ሕዝባዊ ስብሰባ ላይ፣ «ከእኛ ጋር ነው፣ የእኛ ዓላማ አራማጅ ነው ብለው የሚያምኑትን ቡድኖችና ድርጅቶች በሚያስከፋ መልኩ ብዙ እርቀት ተጉዘው ይህን የመሰለ ንግግር አድርገዋል። በመሆኑም እንደ ሞረሽ ወገኔ የዐማራ ድርጅት ዓይነት ላሉ፣ «ዐማራው በዘር ተለይቶ የዘር ማጥፋትና የዘር ማጽዳት ወንጀል ተፈጽሞበታል፤ እየተፈጸመበትም ነው፤ ተደራጅቶ ኅልውናውን ማስጠበቅ አለበት» ብለው ለሚያምኑና ለሚታገሉ ድርጅቶች የቆሙበት መሠረት የጠጠረ አለት፣ የገዘፈ ዕውነት መሆኑን ወዳጅም ጠላትም በግልጽ እንዲያውቀው በማድረጋቸው ምሥጋናችን የላቀ ነው።

ሻለቃ ዳዊት ወልደጊዮርጊስ፣ በስብሰባው ወቅት ንግግራቸውን የጀመሩት፣ በምስለ-ገጽ (ፌስ ቡክ) ከጓደኞቻቸው ጋር የተለዋወጡዋቸውን መልዕክቶች በንባብ በማሰማት ነበር። ማብራሪያቸውን በመቀጠልም የአገር ቤቱ ሕዝብ ከዲያስፖራው መቅደሙን፣ በውጭ ያለው ልዩነት በውስጥ አለመኖሩን፣ የወያኔ ጥንካሬ የተመሠረተው፣ በተቃዋሚው ድክመት እንደሆነ፣ የተቃዋሚው አለመተባበር እንጂ፣ ወያኔ የዐማራውና የኦሮሞው ሕዝባዊ እንቢተኝነት እንቅስቃሴ ተገፍቶ ከሚወድቅበት ደረጃ ላይ እንደነበር አስረድተዋል።

ስለዚህም «ወያኔ ቢወድቅ ምን ማድረግ እንዳለብን ዝግጅት የለንም።» በማለት ደምድመዋል። አያይዘውም «የሽግግር መንግሥት ይመሥረት የሚል ሁኔታ ቢፈጠር፣ ለንግግር ቅረቡ የሚል ጥሪ ቢመጣ፣ ይዘነው የምንቀርበው የጋራ አጀንዳ የለንም። ፉከራና ዲስኩር ብቻ!!! ዝግጅት የለም!!» በማለት «አለን! መጣን! ደርሰናል» በማለት በብዙኃን መገናኛ መሣሪያዎች የሚደነፉትን «ዝግጅት አልባ» ቡድኖችንና ድርጅቶችን ኮንነዋል።

ሻለቃ ዳዊት አዲስ አበባ ውስጥ አንድ የተቋጠረና በቂ ዝግጅት ያለው ድርጅት ቢኖር ኖሮ፣ የኦሮሞውና የዐማራው እንቅስቃሴ ለድል ይበቃ እንደነበር በቁጭ ተናግረዋል። ከሁሉም በላይ የመገናኛ ብዙኃን ባለቤት የሆኑ ቡድኖች «እንቅስቃሴውን የምንመራው እኛ ነን» እያሉ ለእንቅስቃሴው የተለያዩ ስሞች በመስጠት ሲዘገብ የነበረው ውሸት እንደነበር እንዲህ ሲሉ ዕውነቱን በፊታቸው ቆመው አጋልጠዋል። «የጎጃምና የጎንደርን እንቅስቃሴ ማንም የረዳቸው የለም።– እንቅስቃሴውን በኢሣት መረጃ ከመስጠት» በስተቀር የተደረገ ሌላ ነገር አለመኖሩን አጋልጠዋል።

ዳዊት ስለአንድነት አስፈላጊነት ባነሱበት ቦታ ላይ፣ «አናሳ ብሔረሰቦች ከኢትዮጵያዊነት ጋር ጠላትነት የላቸውም። «የኦሮሞ ነፃ አውጭ ግንባር ከኢትዮጵያ የመገንጠል ዓላማ እንዳለው ገልጸው፣ የዚህ ድርጅት አባሎች የነበሩ ሰዎች ዕውነታውን ተረድተውና አገናዝበው ኦዴፍ (የኦሮሞ ዴሞክራሲያዊ ግንባር) የሚል ድርጅት መሥርተው፣ ከኦነግ የመገንጠል ዓላማ ወጥተው፣ ለኢትዮጵያ አንድነት እየታገሉ መሆኑን አስረድተዋል። ለዚህም፣ የኦሮሞውና የዐማራው አንድነት መፈጠር ለኢትዮጵያ አንድነት መሠረት መሆኑን አጽንዖት ሰጥተው የሁለቱን ነገዶች አንድነት አስፈላጊነት የግድ እንደሆነ አስረድተዋል።

ከዚሁ አያይዘው፣ «አገራዊ ንቅናቄው አለ ለማለት አይቻልም። ምክንያቱም ዐማራው ተደራጅቶ አልቀረበም» በማለት ለንቅናቄው ወደፊት መግፋት የዐማራው መደራጀትና ንቅናቄውን መቀላቀል ምርጫ ሳይሆን፣ ግዴታ መሆኑን አልሸሸጉም። ይህንም እንዲህ ሲሉ ያጠናክሩታል። «የዐማራው ሕዝብ በንቅናቄው ውስጥ ካልተወከለ አገራዊ ንቅናቄው አለ ለማለት አይቻልም» በማለት ደምድመውታል። ሻለቃ ዳዊት የትግሬ ወያኔ ከፍተኛ ጥቃት እያደረሰ ያለው በዐማራው ላይ በመሆኑ፣ የዐማራው ሕዝብ ወኪል የሆነ ድርጅት መመሥረት እንዳለበት ያምናሉ። ከሁሉም በላይ ወያኔ አጥብቆ የሚጠላው የኦሮሞንና የዐማራን አንድነት መሆን አውስተው፣ ባንድ ወቅት ሟቹ መለስ ዜናዊ «የዐማራና የኦሮሞ ሕዝብ አንድ የሆነ ዕለት፣ያንጊዜ ‘TPLF’ (ሕወሓት) አለቀለት ማለቱን አውስተዋል።

የዐማራና የኦሮሞውን አንድ መሆን ለኢትዮጵያ አንድነት ዋስትና መሆኑን አስረድተዋል። ዳዊት በዚህ ንግግራቸው፣ «የምናገረው ዐማራ ብሆንም፣ ለዐማራ አይደለም፤ የዐማራው መደራጀት አስፈላጊነትን ነው።» ብለዋል። አያይዘውም እንዲህ አሉ፤ «ኦሮሞው፣ ትግሬው፣ ሶማሌው፣ ሲዳማው፣ ጉራጌው፣ ወዘተርፈ ሲደራጅ አከራካሪ አልነበረም። ዐማራው ይደራጅ ሲባል ጫጫታ ተጀመረ። ለምን ዐማራው ይደራጅ ሲባል የሚንጫጫው ለምንድነው በሉ? — ተልዕኮ አላቸው።» «ዐማራው እየተጠቃ ያለው በፖለቲካ አቋሙ ሳይሆን፣ በማንነቱ፣ በዐማራነቱ ነው። የዐማራው ትግል የመኖር ወይም ያለመኖር ነው።» በማለት የዐማራውን መደራጀት አስፈላጊነትና ለመደራጀቱ ምክንያቱም ምን እንደሆነ በግልጽ ቋንቋ አስረድተዋል። ይበል እንላለን ሻለቃ ዳዊት!

ዳዊት ወልደጊዮርጊስ በዚህ ታሪካዊ ሊባል በሚችል ንግግራቸው የትግሬ ወያኔ ቡድን ዐማራውን አምርሮ እንደሚጠላ እንዲህ ሲሉ አስረድተዋል። «ስብሐት ነጋ፣ ባንድ ወቅት፣ እኛ ወደ መቀሌ ከተባረርን፣ እናንተን (ዐማራውን) መንዝ ላይ አራግፈናችሁ ነው የምንሄደው» ማለቱንና፣ በተመሳሳይ ሁኔታ ሣሞራና መለስ በተከታታይ እንዲህ ማለታቸውን አስረድተዋል። «ገድለን የቀበርነው ዐማራ፣ እንዲያንሰራራ አንፈቅድለትም።» « ዐማራን አከርካሪውን ሰብረን፣ ትከሻውን ለእስክስታ መውረጃ ትተንለት ወደ ቤተ መንግሥት አይገባም።» በማለት በዐማራው ላይ የገነቡት ጥላቻ የቱን ያህል የከፋና የከረፋ መሆን በተጨባጭ ማስረጃዎች አስረድተዋል።

በግልጽ እንደሚታወቀው፣ ከስንዴ መሀል እንክርዳድ፣ ከገብስ መሀል ጎስ፣ ከጥሩ ዝልል መሀል አሰር መገኘቱ አይደንቅም። በሻለቃ ዳዊት ወልደ ጊዮርጊስ የሲያትል ንግግር ውስጥም ተመሳሳይ እንክርዳዶች፣ ጎሶችና አሰሮች አልጠፉም። ለምን እንደዚህ ሆነ ብሎ ሞረሽ ወገኔ የዐማራ ድርጅት ወቀሳ ውስጥ አይገባም። ምክንያቱም ሞረሽ ወገኔ በሂስ፣ በምክር፣ በትችት ያምናል። «የሚስቅልህ ቀባሪህ፣ የሚስቅብህ መካሪህ» በሚለው የአባቶቻችን ይትበሃል በጽኑ ያምናልና!

ሐቁ ይሆኖ ሳለ ግን፣ «አንካሣ የነዛውን ወሬ፣ ባለፈረስ አይመልሰውምና» «ሞረሽ በጽሑፍ ኦሮሞ የሚባል ሕዝብ የለም፣ ከማዳጋሥካር የመጡ ናቸው፣ ብለው ነው የሚያምኑት፣ የኢትዮጵያ ሕዝብ ዐማራ ብቻ ነው» ብለው ጽፈዋል ያሉት ከአክብሮት ጋር ውሸት ነው። ሻለቃ ዳዊት ሞረሽ ወገኔ እንዲህ ብሎ የጻፈበትን ጽሑፍ ለሕዝብ እንዲያቀርቡ በታላቅ አክብሮት ይጠየቃሉ። ይህ የአፍ ወለምታ ከሆነ በግልጽ ሞረሽ ወገኔን ይቅርታ ሊጠይቁ ይገባል።

በሌላ በኩል ዐማራው አልተደራጀም የሚለው አባባል ትክክልም ተገቢም አይደለም። መባል ካለበት፥ በዐማራው ስም የተደራጁት ድርጅቶች በሻለቃ ዳዊት እና በዶክተር ጌታቸው በጋሸው የሚንቀሳቀሰው ንቅናቄ፣ «መለስ ዜናዊ ጠፍጥፎ እንደሠራቸው የነገድ ድርጅቶች በኦዴፍና በግንቦት 7 ቡራኬ የተደራጁ ስላልሆነ አንቀበላቸውም» ቢባል ያስኬዳል። ከዚህ በተረፈ ካንድ በላይ ድርጅቶች በዐማራ ስም ተደራጅተው ድምፃቸውን እያሰሙ መሆኑን ሻለቃ ዳዊት ለማስተባበል አልሞከሩም። እንዲያውም የጎንደር ሕዝብ መደራጀቱን ዘግይተውም ቢሆን ነግረውናል። በዚህ መልክ ለተደራጁት ዕውቅና ሳይሰጡ «አዲስ እናደራጃለን» ማለት ውኃን ወቅጦ ለማላም እንደመጣር ይቆጠራል። ዐማራው ለመደራጀትና ያሻውን ለማድረግ የማንንም ድጋፍም ሆነ ፈቃድ አይጠይቅም። ስለሆነም ዕውቅናም በትግሉ የሚያገኘው ፀጋው እንጂ፣ ከሌሎች በችሮታ የሚያገኘው አይደለም።

ዐማራን ከፈጽሞ ጥፋት እንታደጋለን!

የዐማራው ኅልውና መጠበቅ፣ ለኢትዮጵያ አንድነት መረጋገጥ ዋስት ነው!

17 thoughts on “የሻለቃ ዳዊት የዋሽንግተን ሲያትል ንግግር በሞረሽ ዕይታ!

Leave a Reply