የአፋር ህዝብ መከራ እና አዲሱ የወያኔ የማስቀየሻ ስልት

የአፋር ህዝብ መከራ እና አዲሱ የወያኔ የማስቀየሻ ስልት

ሸንቁጥ አየለ

 

 

የአፋር ህዝብ መከራ እና አዲሱ የወያኔ የማስቀየሻ ስልት
የወደፊቱዋ ኢትዮጵያ

“ኢትዮጲያን መልሶ የቀይ ባሕር ሀይል የሚያደርግ ፖሊሲ ያስፈልጋል” አለ አንዱ የወያኔ ቁንጮ:: ማን ነዉ በል? ጻድቃን ገብረትንሳኤ ነዋ!!

ሆሆ ሆሆ… እነዚህ የማያፍሩ ሀገር ሻጭ እና ሀገር አስገንጣዮች ምንም ነገር ለመናገር አያፍሩም ማለት ነዉ? እንኳን አንዴ ያስገነጠሉትን ኤርትራን ተዋግተዉ ቀይባህርን ሊያስመልሱ ይቅርና አሁንም በየቀኑ ከኢትዮጵያ ምድር ላይ ሀገር እየከፈሉ በግድ ለጎረቤት አገር የሚሸጡ ሀገር ሻጭ ባንዶች አሁን ስለ ባህር ወደብ ማላዘን ጀምረዋል::

ነገሩ ማስቀየሻ መሆኑ ነዉ:: ምናልባትም በጓዳ ከሻቢያም ጋር ተነጋግረዉ አድርገዉት ሊሆን ይችላል:: ወጣም ወረደም ግን በዚህ ሰዓት እንኳን ከጎንደር መሬት ላይ እየቆረሱ ለሱዳን የሚሰጡ የኢትዮጵያዊነት እና የኢትዮጵያ ጠላት ወያኔዎች እንዲህ አይነት ትልቅ ሀገራዊ ተልዕኮ የሚሸከም ትከሻም ሆነ ልብ እንደሌላቸዉ ይታወቃል:: የቀይ ባህር ወደብን ማስመለስ ከነዚህ ሰዎች ስነልቦና ጭብጥ ጋር በእጅጉ የተጣላ ነዉ::

ወያኔ እንዲህ የማስቀየሻ ወሬዎቹን አንዴ በተገለሉ ጀነራሎቹ : አንዴ ቢሮ አንቀዉ በያዙ ፕሮፖጋንዲስቶቹ ሲነፋ ኢትዮጵያዊዉ ህዝብ ግን በምስራቅም: በምዕራብም : በደቡብም : በሰሜንም ብሎም በመሃልም መከራዉን እያዬ ነዉ::

ጠረፍ ላይ ያለዉ የአፋር ህዝብ በቀይ ባህር ላይ አሳ አጥምዶ : ጥቃቅን የኑሮ እንቅስቃሴዎቹን ከልዩ ልዩ ንግዶች ጋር አስተሳስሮ የሚኖር ኢትዮጵያን የሚወድ ታላቅ ህዝብ ነዉ::በዕሻቢያ ስምምነት ቀይባህር ላይ የከተመዉ የሳዉዲ አረቢያ ሀይል ግን ይሄን የአፋር ህዝብ ለምን በቀይባህር ላይ አሳ ታጠምዳለህ? ለምን የቀይ ባህር ዉሃ ላይ ጀልባ ትነዳለህ? እያለ በጦር አዉሮፕላን እየደበደበዉ ነዉ:: በሻቢያም ሆነ በወያኔ በጠላትነት የተፈረጀዉ የአፋር ህዝብ ማንም ሀይ ባይ እና ደራሽ ወገን የለዉም:: አፋር ኢትዮጵያን እና ኢትዮጵያዊነትን በመዉደዱ የሚከፍለዉ መከራ ብዛቱ ተቆጥሮ አያልቅም::

ኢትዮጵያ ዳር ድንበሯ የተከበረ ቢሆን ኖሮ: የቀይ ባህር ጠረፎቿ ከዉስጥ እና ከዉጭ በተሰለፉ ጠላቶቿ ባታጣዉ ኖሮ ዛሬ ኢትዮጵያዊዉ አፋር በመሬቱ ላይ እና በቀይ ባህር ጠረፎች ላይ እንዳሰኘዉ ኑሮዉን መመራት ይችል ነበር::የአፋር ህዝብን በማዋረድ እና በመቀጥቀጥ በቀጣናዉ ላይ ገናና መሆኑን ለማስመስከር ያቀደዉ የሳዉዲ አረቢያ ልዕለ ሀያልነት መነሻ እና መድረሻዉ ግን መላዉን የኢትዮጵያ አንገት አንቆ በመያዝ ለወደፊቱ ገባሪ ማድረግ ነዉ:: ይሄም ይሰምር ዘንድ መጀመሪያ የኢትዮጵያ ጠረፎችን በቁጥጥር ስር ማድረግ ብቻ ሳይሆን ኢትዮጵያዉይኑን በጦር ጀት እየደበደቡ ማዋረድ ዋናዉ ተልዕኮ ነዉ::

የኢትዮጵያን የንግድ እንቅስቃሴ እና አለም አቀፍ ግንኙነት አንቆ በሚይዝ መልክ ኢትዮጵያም ሀገር እንዳልሆነች ሁሉ እንደ ሰፈር እድር በወያኔ እና ሻቢያ ስትገነጣጠል ብሎም ህዝቦቿ እንደ አንድ ህዝብ ሳይሆን ድንገት በአጋጣሚ እንደተገናኙ የማይተዋወቁ የጎሳ ስብስብ ተደርገዉ እንዲዋረዱ ሲደረግ በእያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ማህበረሰብ ላይ መከራ እንደሚመጣ ተደጋግሞ ተወስቷል:: እናም እየሆነ ያለዉ ይሄዉ ነዉ::ወያኔም በዚህ ህዝባዊ መከራ ላይ ሁሌ እያላገጠ አዳዲስ አጀንዳዎችን ለማስቀየሻነት ይመዝበታል::

ዛሬ ኦሮሞዉ በምስራቅ ሰላም የለዉም:: ሶማሌዉ በራሱ ነገዶች ተከፋፍሎ መከራዉን ይጠብሳል::አፋሩ ከላይ እንደተባለዉት በራሱ የቀይባህር ጠረፍ እና ዉሃ ላይ በሳዉዲ አረቢያ በጀት ይደበደባል ይደብደደባል:: በምዕራብ ኢትዮጵያ ጋንበላዉ እርስ በርሱ እንዲገዳደል የማያሰልስ የቤት ስራ ዉስጥ እንዲወድቅ ተደርጓል::አማራ በመላ ሀገግሪቱ መከራዉን ይጠብሳል:: ኢትዮጵያዊ ሁሉ መሸሸጊያ እና መግቢያ ያታጣባት ምድር ተፈጥራለች:: በሀገር ዉስጥ እና በሀገር ዉጭ ጠላቶች የታነቀ ብሎም ለወዳጅ ማፈሪያ ለጠላት መዘበቻ የሆነበት ሁኔታ በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ ወድቋል::ኢትዮጵያዊነት ብሄረተኝነት የዉርደት ማቅ ለብሶ በአርምሞ ዉስጥ ሰጥሟል::

እናም የወያኔ ስትራቴጅስት ጀነራሎች እነ ጻድቃን በዚህ ሁሉ የኢትዮጵያ ህዝብ ድቀት እና መከራ ላይ እየዘበቱ አዳዲስ የማስቀየሻ ስልታቸዉን ይዘዉ ብቅ ይላሉ:: “ኢትዮጲያን መልሶ የቀይ ባሕር ሀይል የሚያደርግ ፖሊሲ ያስፈልጋል” አለና የተገለለዉ የወያኔ ጀነራል ጻድቃን ገብረትንሳኤ::ይሄን ከመናገሩ በፊት ግን ስለኢትዮጵያ እና ስለኢትዮጵያዊነት መከራ እና ዉርደት ለመናገር አይደፍርም:: ለምን ቢሉ? የእርሱ ሀሳብ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት ወደ ክብር ማማ ላይ የሚወጡባት ጉዳይ ላይ ትኩረት ማድረግ ሳይሆን ኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያዊነት የሚደናገሩበት ነጥብ መዝራቱ ላይ ነዉ:: በእርሱ ቤት አሁን ማስቀየሻ አጀንዳ መስጠቱ ነዉ::

የጎንደርን መሬት ከእግር እስከ ወርዷ ሸልቅቆ ለሱዳን ሲሰጠዉ በደስታ ዝምታ ዉስጥ የተመሰጉት የወያኔ የክፉ ቀን ጀነራሉች (እነ ጻድቃን) አሁን የቀይባህርን ጉዳይ እንደ ካርድ ይዘዋት መጥተዋል::

የአፋር ህዝብ በሳዉዲ ጀቶች ሲደበደብ እና መሄጃ አጥቶ የመኖሪያ ህልዉናዉ አደጋ ላይ ተጋርጦ እንኳን አንድ ቃል የማይተነፍሱት ወያኔዎች አሁን ስለቀይባህር አጀንዳ ይዘዉ መምጣታቸዉ ክብር የስነልቦና ይዘታቸዉ ለኢትዮጵያ ህዝብ ቀርቶ ለራሳቸዉ ክብር እንደሌላቸዉ ይመሰክራል::

በወያኔ አይን የአፋር ህዝብ ዋጋ የለዉም::እንዴዉም ጠላት ነዉ:: ይሄ ህዝብ ከኢትዮጵያዊነት እና ኢትዮጵያ ጋር የተጣበቀ እና ኢትዮጵያዊነትን የሚወድ ነዉና ለወያኔ የዚህ ህዝብ በሳዉዲ ጀቶች መደብደብ ምንም ትርጉም አይሰጣትም:: እንዴዉም ማስተባበያ ይሰጡበታል::በሳዉዲ ጀቶች የሚደበደቡት አፋሮች ኤርትራ ምድር ዉስጥ ያሉት ናቸዉ ብለዉ ክብረ ቢስ ማስተባበያ ሊሰጡ ይችላሉ::

የቀይ ባህር ምድር በሙሉ እና የኤርትራ መሬት በጠቅላላዉ የኢትዮጵያዉያን መሆኑን የሚቀበል ስነልቦና ስለሌላቸዉ ኢትዮጵያዊዉን ህዝብ እና ኢትዮጵያዊዉን መሬት ሁሉ ጠቅልለዉ አስገንጥለዉ ለስልጣን መወጣጫ ካሳነት ሸጠዉታልና:: የሆነ ሆኖ ግን ከቀይባህር በፊት ስለ ኢትዮጵያዊዉ አፋር ህዝብ መጮህ ግድ ነበር:: ስለኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያዊነት የድንበር ክብር: የህዝብ ክብር እና የአጠቃላይ ሀገራዊ ህልዉና ክብር መጮህ እና መናገር ግድ ነበር::

ኢዮብ ብርሃነ ጥሩ አድርጎ እንደገለጸዉ “ገንጣይ እና አስገንጣዮች የችግራችን ምንጮች እንጂ የመፍትሔው አካል አይሆኑም:: ይልቅስ የአፋር ሕዝብን እርስበርሱ በጎሳ ማጋደሉን፤ አፋርን ከአማራ፣ ከኦሮሞ፤ ከአርጎባ፤ እንዲሁም የአፋር ሃብትን መመዝበርና የአፋር ወረዳዎች ሸርፎ ወደ ትግራይ ማስፋቱን ተውት” ቢላቸዉ ያስመሰግነዉ ነበር::

በአጠቃላይ በአፋር ህዝብ መከራ ላይ ብሎም በኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያዊነት ዉርደት ላይ የሚያላግጠዉ ወያኔ ስለ ቀይባህር ያነሳዉ የሰሞኑ ነጥብ አዲሱ የማስቀየሻ ስልት ብቻ ነዉ::