የጥንታዊ ኢትዮጵያዉያን የጠፈር ምርምርና ግንዛቤ

የጥንታዊ ኢትዮጵያዉያን የጠፈር ምርምርና ግንዛቤ

በምእራባውያኑ የስነህዋ የምርምር ተቋማት black hole በመባል ስለሚጠሩት ምስጢራዊ ቦታዎች NASAን ጨምሮ የተለያዩ የፊዚክስ ምሁራን የራሳቸውን መላ ምት በመዘርዘር የቦታውን ምስጢራት ለመፍታት የሞከሩ ሲሆን አልበርት አንስታይን በግንባር ቀደምትነት ይጠቀሳል፡፡ በዚህ ጽሁፍ ላይ የምእራባውያኑን ምሁራን ንድፈ ሃሳብ ሳላብራራ በቀጥታ ቀደምት ኢትዮጵያውያን አባቶች እና የጽሁፍ ዶክመንቶች ስለነዚህ ምስጢራዊ ቦታዎች የተናገሩትን የተለያዩ እውቀቶች በአንድ በማጣመር ለማስረዳት እሞክራለሁ፡፡ አንባብያን ይህን የኛን ንድፈ ሃሳብ ከእምራባውያኑ ጋር በማገናኘት እና በማነጻጸር አንድ ነጥብ ላይ ለመድረስ መንደርደሪያ እንደሚሆናችሁ አምናለሁ፡፡

ቀደምት ኢትዮጵያውያን አባቶች እንደሚያስተምሩት አለማት አራት ሲሆኑ የእሳት የምድር የንፋስ እና የውሃ ዓለማት ይባላሉ፡፡ የእሳት ዓለማት የሚሰኙት ዘጠኝ ዓለማት ሲሆኑ የምድር ዓለማት የሚባሉት ደግሞ አምስት ዓለማት ናቸው፡፡ በነዚህ ሁለት ዓለማት ውስጥ በሚገኙት አስራ አራት ዓለማት ውስጥ የተለያዩ ፍጥረታት ይኖራሉ፡፡ እነዚህ የአስራ አራት ዓለማት ፍጥረታት ማለትም የእሳት ዓለማት የሆኑት ዘጠኝ ዓለማት እና አምስቱ ምድራዊ ዓለማት ውስጥ የሚገኙት ፍጥረታት አንዳቸው ከአንዳቸው ግንኙነት የሚፈጥሩባቸው አስራሁለት የተለያዩ ቦታዎች አሉ፡፡ ምእራባውያኑ የስነህዋ ምሁራን black hole ብለው የሚጠሯቸው ከነዚህ አስራ ሁለት ቦታዎች ስድስቱን ቦታዎች ነው፡፡

ይህን ከማብራራቴ በፊት ስለአስራ አራቱ ዓለማት ፍጥረታት እና ስለዓለማቱ ባህርያት ማብራራት ተገቢ ነውና በቀጥታ ወደዛ አመራለሁ፡፡ የእሳት ዓለማት የሚባሉት ጽርሃ አርያም( ኢትዮጵያ እና ቤተክርስትያን የጽርሃ አርያም ተምሳሌት ናቸው) (መንበረ መንግስት) (ሰማየ ውድውድ)( ኢየሩሳሌም ሰማያዊት) (ኢዮር) (ራማ) (ኤረር) ምጽናተ ሰማይ( ባህረ እሳት) (ገሀነመ እሳት) ናቸው፡፡ በዓለመ እሳት ከሚገኙት ሰማያት ሶስቱ ቅዱሳን መላእክት የሚኖሩባቸው የመላእክት ከተሞች ሲሆኑ ኢዮር ራማ ኤረር ይባላሉ፡፡ ኢዮር በተሰኘው የመላእክት ከተማ አራት የመላእክት ነገዶች ይኖራሉ፡፡ እነርሱም አጋእዝት ኪሩቤል ሱራፌል እና ኃይላት ይሰኛሉ፡፡ የአጋእዝት ነገድ አለቃ ሳጥናኤል ይባላል እንዲሁ የኪሩቤል አለቃ ገጸ ሰብ እና ገጸ አንበሳ ሲሆን የሱራፌል ነገደ መላእክት ገጸ ንስር ሲሆን በስተመጨረሻም የኃይላት ነገደ መላእክት አለቃ መልእኩ ቅዱስ ሚካኤል ነው፡፡ በራማ በሚገኘውም የማላእክት ከተማ ሶስት ነገደ መላእክቶች ይኖራሉ የነገዳቸውም ስም መናብርት አርባብ እና ሥልጣናት ይባላሉ፡፡

የመናብርት አለቃ መልአኩ ቅዱስ ሩፋኤል ሲሆን የአርባብ ነገደ መላእክት አለቃም እንዲሁ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ነው በመጨረሻ የሚገኘው የስልጣናት ነገደ መላእክት አለቃ መላእኩ ቅዱስ ሱርያል ነው፡፡ በሶስተኛው የመላእክት ከተማ ኤረር ሶስተ ነገደ መላእክት ይገኛሉ የነገድ ስማቸው መኳንንት ሊቃናት እና መላእክት ይሰኛሉ፡፡ የመኳንንት አለቃ መልአኩ ቅዱስ ሰዳካኤል ሲሆን የሊቃናት መልአኩ ቅዱስ ሰላትኤል በስተመጨረሻም የመላእክት ደግሞ መልአኩ ቅዱስ አናንያኤል ነው፡፡
ምድራዊ ሰማያት የሚባሉት ገነት ብሔረ ሕያዋን ብሔረ ብጽአን መሬት እና ሲኦል ሲሆኑ ሰማያት እኛ የምንኖርባት ምድር ከመሃል የምትገኝ ሲሆን ገነት በምስራቅ በኩል ብሔረ ሕያዋን በሰሜን ብሔረ ብጹዓን በስተደቡብ ይገኛል ሲኦል በምእራብ በኩል ይገኛል፡፡

ከላይ የጠቀስናቸው አስራሁለት ቦታዎች በእሳት ዓለማት ውስጥ የሚገኙት ሰማያዊ ሃይላትና በምድራዊ ሰማያት እና በንፋስ ዓለማት ውስጥ በሚገኙ የሰዎች ፍጥረታት እና የስማዝያ እና የሳጥናኤል ጭፍሮች ግንኙነት የሚፈጠርባቸው ምስጢራዊ መንፈሳዊ ቦታዎች ናቸው፡፡ እነዚህ ቦታዎች ለሁለት የሚከፈሉ ሲሆን የመጀመርያው ስድስቱ ቦታዎች ክፉ መናፍስት ከአንደኛው ዓለም ወደሌላኛው ዓለም ግንኙነት የሚፈጥሩባቸው እና የሃይላቸው ማረፊያ የሆኑ ቦታዎች ሲሆኑ እንደ ምእራባውያኑ አገላለጽ black hole የሚባሉት ቦታዎች ናቸው፡፡ የተቀሩት ስድስቱ ደግሞ ቅዱሳን የሆኑ ሰማያዊ ሃይላት ለመልእክት እና ለአገልግሎት የሚወጡባቸውና የሚወርዱባቸው ብሎም ማደሪያቸው የሆኑ ቅዱሳን ቦታዎች ናቸው ስለዚህ ለመረዳት እንዲያመቸን በነጮቹ አገባብ እኛ እነዚህ ቦታዎች WHITE HOLE ብለን ልንሰይማቸው እንችላልን፡፡

በዚህ black hole ምስጢራት ላይ ለሚደረገው ጥናት ለምእራባውያኑ ፍንጭ የሰጠው Einstein’s general relativity (GR) ንድፈ ሃሳብ ቢሆንም ከአልበርት አንስታይን ንድፈ ሃሳብ በተሻለ ግን ስለቦታዎቹ ማብራረት የሚቻለው መጽሀፈ ራዚኤል ወይም ህይወት መጽሀፍ ብለን የምንጠራው መጽሀፍ ሲሆን ይህ መጽሀፍ በአራቱ ሰማያት መካከል ያለውን የሃይል የጊዜ እና የግዝፈት ልዩነት ያስረዳል፡፡ ይም መጽሀፍ አዳም የጻፈው መጽሀፍ ሲሆን አዳም የበእሳት ዓለማት ውስጥ የሚገኙት ቅዳስን መላእክት ያስተማሩትን ጥበብ ያሰፈረበት ነው፡፡ አዳም እኛ በምንኖርባት ምድር እና በገነት መካከል ያለውን የሃይል የጊዜ እና የግዝፈት ልዩነት ውጭ ሆኖ በሁለቱም ዓለማት ላይ መኖር የቻለው መላእክቱ ባስተማሩት ጥበብ፡፡ ይህም አዳም ገነት በኖረበት ሰባት ዓመት እና በምድር 2555000 ሚሊየን ዓመት መካከል ያለውን የሃይል የግዝፈት እና የጊዜ ልዩነት አስማምቶ መኖር ችሏል፡፡ በዛም መሰረት አዳም ወደምድር ሲመጣ ሰባት አመት እንዳሳለፈ ሰው እንጂ በምድራዊ የጊዜ አቆጣጠር 2555000 ሚሊየን ዓመት እንዳሳለፈ ሰው ሆኖ አይደለም ወደምድር የመጣው፡፡

እንደ ኢትዮጵያውያን አባቶች አስተምህሮት ከላይ በሁለት ምድብ በከፈልናቸው black hole(የክፉ መናፍስት የሃይል ማደርያ) እና WHITE HOLE( የእሳት ዓለማት ውስጥ የሚገኙት የቅዱሳን መላእክት ማደርያ) የሆኑት እነዚህ ቦታዎች በአራቱ ዓለማት ውስጥ ከሚገኙት የሃይል የጊዜ እና የግዝፈት ልዩነት ውጭ ናቸው፡፡ በዚህ የተነሳም እነዚህ ቦታዎች ከመሬት ስበት ህግ ውጭ የሚሆኑበት እድላቸው ሰፊ ነው፡፡ የእሳት ዓለም ፍጡራን የሆኑት ቅዱሳን መላአክት ከሰው ልጆች ጋር ግኑኙነት የሚፈጥሩባቸው እና የሃይላቸው ማደርያ የሆኑት ስድስት ቦታዎች በምድር እና በእሳት ዓለም ብሎም በብሔረ ሕያዋን ሰማያት መካከል ካለው የሃይል የጊዜ እና የግዝፈት ልዩነት ውጭ ሲሆኑ እነዚህ ቦታዎች ለተቀደሰ መንፈሳዊ ስራ የሚተጉባቸው ቦታዎች (WHITE HOLE) ናቸው፡፡ ከዚህ በተቃራኒው ስድስቱ የክፋት ቦታዎች ከጊዜ ከሃይል እና ከግዝፈት ውጭ የሆኑት ቦታዎች ክፉ መናፍስት የሆኑት የስማዝያ እና የሳጥናኤል ጭፍሮች አንዳቸው ከአንዳቸው ብሎም የክፉ ስራቸው አባሪ ከሆኑ የሰው ልጆች ጋር ግንኙነት የሚፈጥሩባቸውና የክፋት የመንፈስ ስራ የሚሰሩባቸው ( black hole) ቦታዎች ናቸው፡፡
ይህ በኔ የአስተሳሰብ ልኬታ ስለተጻፈ ለሁሉም ሰው አጥጋቢ ሊሆን ባይችልም ሰፋ ያለ ጥናትን ማድረግ ለሚሻ ሰው ሀገራዊ በሆነው እውቀት ላይ ግን ፍንጭ የሚሰጥ ይመስለኛል፡፡
ምንጭ፡ ኦሪት ዘፍጥረት አንድምታ
፡ መጽሀፈ ሄኖክ
፡ መጽሀፈ ራዚኤልን ከተረዱ አባቶች ጋር ያደረኩት ቆይታ
፡ Einstein’s general relativity (GR)

 

ጥልቅ የሆነ የኢትዮጵያውያን የስነ ህዋ እውቀት

እንደ ኢትዮጵያውያን ሊቃውንት አስተምህሮ መሰረት ፀሐይ: ከእሳት እና ከነፋስ ውህደት ጨረቃ: ከነፋስ እና ከውሃ ውህደት ከዋክብት ደግሞ ከነፋስና ከውሃ ውህደት ተፈጥረዋል።

ይሄ ተረት ተረት አይደለም። ይሄ እጅግ ጥልቅ የሆነ የኢትዮጵያውያን የስነ ህዋ እውቀት አልያም አገራዊ ሳይንስ ነው። ይህን ለመቀበል አልያም በዚህ ፍልስፍና ላይ ሰፊ ተግባራዊ ጥናቶችን ለማድረግ የነጮችን ይሁንታ መጠበቅ የለብንም። ከላይ የተጠቀሰውን እና ተያያዥ ኢትዮጵያዊ የስነ ህዋ እውቀቶች ላይ ዘመኑ በሚፈልገው መስፈርት ተግባራዊ ጥናቶችን በማድረግ አገራዊ እውቀቶችን ግራ ለተጋቡት የአለም ምሁራን ማስተማር የኛ ሀላፊነት ነው። በተለይ ወጣት ሙያተኞችና ተማሪዎች የጥንቱን አገራዊ እውቀት ወደአሁን እና ወደፊት ለማምጣት ትኩረት ማድረግ አለብን። ትኩረት ማድረግ አለብን! !!!!

ከላይ የተጠቀስኩት የስነህዋ እውቀት በሚከተሉት መፅሀፍት ላይ ተተንትኗል።
፩, የስነ ፍጥረት አንድምታ
፪, መፅሐፈ አክሲማሮስ

ተያያዥ መፃህፍት
√ መፅሐፈ ሔኖክ
√ አቡሻህር

እነኚህ መፃህፍት ለመግዛት ከሆነ በመንፈሳዊ መፃህፍት መደበር ለማንበብ ከሆነ ፒያሳ በሚገኘው የገነተ ፅጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤ/ክ ሰንበት ት/ቤት ቤተመፃህፍት ውስጥ ይገኛል።
ገዝታችሁ አልያም ቤተመፅሀፍት ገብታችሁ በማንበብ ለአበው እውቀት ዋጋ እንደምትሰጡ ተስፋ አደርጋለሁ።

‪#‎ራፋቶኤል‬