የኩሽ ፖለቲካ ቀመር ግብ

የኩሽ ፖለቲካ ቀመር ግብ
የኩሽ ፖለቲካ ቀመር ግብ

ሰሞኑን የኦነግ መሥራች አባሎችና ተከታዬቻቸው አዲስ አጀንዳ ይዘው ብቅ ብለዋል:: ይህም አጀንዳ የኩሽቲክ ቁዋንቁዋ መሠረት ያላቸውን ነገዶች በኦነግ ፍላጎት ሥር ለማዋል የታቀደ እንደሆነ ድርጊቱ በግልጽ ያመላክታል:: የማስታዎስ ችሎታችን የቅርብ የቅርቡን ካልሆነና የሩቁንም ካስታዎስን የኦነግ ዓላማ ከኢትዮጵያ መገንጠል ነው:: ለዚህ ዓላማው ዕውን መሆንም በቅድሚያ የነባር የነገዱን ስም ለውጦ “ኦሮሞ” ነህ በማለት በዚህ አዲስ ማንነት ሕዝቡን ማሳመን ቀጥሎ የኢትዮጵያ ታሪክ የማያውቀው “ኦሮሚያ” የተባለ ግዛት በመፍጠር በተለያዩ ክፍለ-ሀገሮች ወይም ጠቅላይ ግዛቶች ይኖሩ የነበሩትን የነገዱ አባሎች አዲስ የኦሮሞነት ሥነልቦና ባህል ወግና ትርክት እንዲላበሱ ማድረግ ተቀዳሚ ተግባራቸው አድርገው ተንቀሳቀሱ::

እንቅስቃሴአቸውም ኢትዮጵያ እንድትበታተን በሚሹ ኃይሎች ሁለንተናዊ ድጋፍ ኦሮሞ የሚለውን መጠሪያ ከሰጣቸው ጀርመናዊ ሰላይ ዮሐን ክራፍ በመዋስ በመኢሶኑ መሪ ኃይሌ ፊዳ አማካኝነት ደርግ እንዲቀበለው በማድረግ ስሙን አጸኑ:: በወቅቱ ለምን ያለም አልነበር:: “ከሞኝ በራፍ ሞፈር ይቆረጣል” ነውና ሞኙ ኢትዮጵያዊ የስሙ ለውጥ ሊያስከትል የሚችለውን መዘዝ ባለመረዳት ፖለቲከኞቹ ጥሩን ያሉትን ስም አጸደቀ:: ካሁን በሁዋላ መንገዱ ለኦነግ አግድመት ሆነለት::

የነገዱን መጠሪያ ስም ቅቡልነት ካረጋገጠ በሁዋላ ሁለቱን ጥያቄዎች አስከተለ:: እነዚህም ኦሮሚያ የተባለ ግዛትና ኦሮሚኛ የአገሪቱ የሥራ ቁዋንቁዋ የማድረግ ናቸው:: ለእነዚህ ጥያቄዎችም እውን መሆን በኦሮሞ ስም የተደራጁ ድርጅቶች ከትንሽ እስከ ትልቅ ያሉት በመናበብ ኦሮሚያን አገር አድርጎ የመውጣት ሀሳባቸውን ገፉበት:: በዚህም መሠረት ሻዕቢያና ሕወሓት ከሌሎች ፀረ ኢትዮጵያ ኃይሎች ጋር በመሆን የደርግን መንግሥት በማዳከም የአንድነት ኃይሉን በመከፋፈል ወደ ማዕከላዊ መንግሥት መንበር መቃረባቸውን እርግጠኛ በሆኑበት በ1970ዎቹ መገባደጃ ላይ ሦስቱ ፀረ ዐማራና ፀረ ኢትዮጵያ ድርጅቶች ተሰኔ ላይ በመሰብሰብ “የተሰኔ ማንፌስቶ” የተሰኘውን የስምምነት ሰነድ አጸደቁ::

የሰነዱ ዋና ጭብጥ ለኤርትራ መገንጠል እውቅና በመስጠት ቀሪዋን ኢትዮጵያ በነገድ ከፋፍለው ለመግዛት በሚያስችለው ላይ ያነጣጠረ ነበር:: በዚህም መሠረት በሰኔ 24/1983 ሰማኒያ ሰባት ፀረ ዐማራና ኢትዮጵያ የሆኑ ቡድኖች አጸደቁት የተባለውን የሽግግር ወቅት ቻፕተር ሆኖ ያገለገለውን ሰነድ እንዲያዘጋጅ ለሌንጮ ለታ ተሰጠው:: ይህም አጋጣሚ ኦሮሚያ የሚባል ግዛት ለመመሥረት አልሞ ሲንቀሳቀስ ለነበረው ኦነግ ሠርግና ምላሽ ሆነለት:: በመሆኑም ከኤርትራ በመለስ ያሉትን ክፍለ ሀገሮች በቁዋንቁዋ ትስስር ላይ በተመሠረተ አደረጃጀት በአሥራ አራት ክልሎች ሸንሽኖ አቀረበ:: ለመጀመሪያ ጊዜ ማለትም እስከ 1987 ድረስ ክልሎቹ የሚጠሩት በቁጥር ነበር:: እነዚህም:-

§ ክልል አንድ ትግራይ

§ ክልል ሁለት አፋር

§ ክልል ሦስት ዐማራ

§ ክልል አራት ኦሮሚያ

§ ክልል አምስት ሶማሊያ

§ ክልል ስድስት ቤንሻጉል ጉምዝ

§ ክልል ሰባት ጉራጌ

§ ክልል ስምንት ሲዳማ

§ ክልል ዘጠኝ ወላይታ

§ ክልል አሥር ባስኬቶ

§ ክልል አሥራ አንድ ከፍቾ

§ ክልል አሥራ ሁለት አኝዋክ

§ ክልል አሥራ ሦስት ሐረሪ

§ ክልል አሥራ አራት አዲስ አበባ ብለው ሰየሙ:: ይህ መለማመጃ ነበር::

ይህም “ለራስ ሲቆርሱ አያሳንሱ” የሆነለት ሌንጮ ለታ ሠፊውን እና ለሙን ያገሪቱን ክፍል “ኦሮሚያ” ብሎ ለከለለው ክልል አደለ:: ይህ ስያሜ ፀረ ኢትዮጵያ በሆኑ ቡድኖች በሁዋላ ላይ ዛሬ የሚታየውን አምስቱን ክልሎች በአንድ በማጠፍ “የደቡብ

ብሔር ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች” ክልል በማለት የአቅጣጫ ስም ሰጥቶ ሲያደራጅ የቀሩትን በተከታታይ ትግራ አፋር ዐማራ ኦሮሚያ ሶማሊያ ቤንሻጉልብጉምዝ ጋምቤላ ሐረሪ በማለት በክልሎቹ ይኖራሉ ተብለው ከሚታወቁት በቁጥር ብዛት አለው ብለው ባሉት ነገድ ስም እዲጠራ ተደረገ:: የክልሎቹ ዋና ባለቤትም ከዓማራው በስተቀር የክልሉ መጠሪያ የሆነው ነገድ እንዲሆን አደረጉ:: አዲስ አበባ እና ድሬደዋ ግን የብዙ ነገዶች መነኻሪያና መኖሪያ በመሆናቸው ምክንያት ራሳቸውን የቻሉ የከተማ መስተዳፍሮች እንዲሆኑ ሆነ::

ይህም ድልድል ኦነግ የኦሮሚያ መንግሥት እመሠርታለሁ ብሎ ከግማሽ ምዕተ ዓመት በላይ የታገለለት ኦሮሚያ የተሰኘ የኢትዮጵያ ታሪክ የማያውቀው አስዲስ ግዛት ከእጁ ላይ እንዲወድቅለት በማድረግ ወያኔና ሻዕቢያ የድል አክሊል አጠለቁለት::

“ብልጥ ልጅ የሰጡትን ይዞ ያለቅሳል” እንደሚባለው ኦሮሞ የሚለውን ስም እና ኦሮሚያ የሚባለውን ግዛት በእጁ ካደረገ በሁዋላ የኦሮምኛ ቁዋንቅዋ የሥራ ቁዋንቁዋ መሆን አለበት የሚለውን ቀዳሚ አጀንዳው አድርጎ ከመያዝ በተጨማሪ ኦሮሞው በቁጥሩ ብዙ ስለሆነ የፖለቲካው የበላይ መሆን አለበት የሚለውን በነገዱ ዙሪያ ማስረጽ ዋና ተግባሩ አድርጎ ወሰደ:: በዚህም የተለያዩ ድርጅቶችን በመፍጠር በነዚህ ዓላማውች ዙሪያ ተግተው እንዲሠሩ አደረገ::

ወያኔ በተከተለው አግላይና ዘረኛ አቁዋሙ እንዲሁም በፈጠረው የፓርቲና የመንግሥት ውኅደት ያስከተለው ድርጅታዊ ምዝበራና መሬት ቅርምት በሕዝቡ ላይ ያሳደረው ሁሉ አቀፍ ግፍና መከራ የወለደው ሕዝባዊ አመጽ የትግሬ ወያኔ ቡድን ከፖለቲካው ዕምብርት እንዲርቁ ማድረግ ኦሕዴድ የተሰኘው መለስ ዜናዊ እንዳለው “እንደ ፈጣን ሎተሪ ሲፋቅ ኦነግ” ነው የተሰኘው ቡድን ወደ ፖለቲካው ማማ ላይ እንዲወጣ ምቹ ሁኔታን ፈጠረ:: ይህም የኦነግን ዓላማ ዳር መድረስ ያበሰረ ሆነ::

በመሆኑም በኦሮሞ ስም ተደራጅተው በውስጥም በውጭም ይታገሉ የነበሩት የእኛ መንግሥት በሚል ስሜት ድሮም የዓላማ ልዩነት ያልነበራቸው በፍጥነት አዲስ አበባ በመክተት ታሳቢ አድርገው ይዘዋቸው የነበሩትን ሁለት አማራጭ ሀሳቦች ማብላላት ያዙ:: እነዚህም አንደኛ ኢትዮጵያን በኦሮሞ የበላይነት መግዛት ከቻልን ኢትዮጵያን በእኛ ፍላጎት ትርጉም ሰጥተን በአንድነት መቀጠል ይህ ካልሆነ ኦሮሚያን ገንጥሎ አገር ሆኖ መውጣት የሚሉት ናቸው::

እነዚህን ሀሳቦች ፈጭተው ሲያቦኩዋቸው ሊጎረስ የሚችል አጥጋቢ እንጀራ ከምጣዱ ሊወጣ እንደማይችል ተገነዘቡ:: ምክንያቱም ብቻችን በኦሮሞ የበላይነት ኢትዮጵያን እንግዛ የሚለው ሀሳባቸው ብዙም ሊያራምዳቸው እንደማይችል ተገነዘቡ:: የቀራቸው አማራጭ ኦሮሚያን መገንጠ የሚለውን ሲፈትሹ ኦሮሚያ በምሥራቅ በሶማሊያ እና በሐረሪ በደቡብ እና በደቡብ ምራብ በደቡብ ብሔር ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች በምዕራብ በጋብቤላ በሰሜንም ምዕራብና ሰሜን በዐማር የተከበቡና መተናፈሻ የሌላቸው መሆኑ አጤኑ:: ለዚህም መውጫ መንገድ ማፈላለግ ጀመሩ::

አፈላልገው ያገኙት መውጫ በር የኩሼቲክ ቁዋንቁዋ ዘር ወይም ግንድ ያላቸውን ሶማሌዎችን አፋሮችን ወላይታዎችን ሲዳማዎችን ሐዲያዎችን ከምባታዎችን አገዎችን ወዘተ ባንድ የጋራ ቁዋንቁዋ መነሻ ሀሳብነት አማሎ ሁሉም በኦነግ ፍላግት ተመርቶ አንድነቱን እንዲጠየፍና ሴሜቲክ የቁዋንቁዋ ዘር ያላቸውን ትግሬ ዐማራ ሐረሪ ጉራጌና መሠል ነገዶችን በማግለል የራስን አገር መመሥረት የሚለውን ወደ ሕዝቡ ለማስረጽ በየአካባቢው ሲንቀሳቀሱ ይታያሉ:: የዚህ እንቅስቃሴ ፀረ ሴሜቲክ ከመሆኑም በላይ የኒሎቲክ እና የኦሞቲክ ቁዋንቁዋ ዘር ያላቸውን የሚያገልና ጭራሹን ኅልውናቸውን የሚፈታተን እንደሆነ ሊስተዋል ይገባል::

የሰው ልጅ ካንድ ጊዜ በላይ ከተሞኜ ወይም ከተታለለ ያሰው ቂል ነው:: የኢትዮጵያም ሕዝብ ለዚህ የኩሽ ስብስብ ምሥረታ ኅሊናውን ከሰጠ ኢትዮጵያ ያልቅላታል:: የሚያልቀው ደግሞ ሳናውቅ ሳይሆን እየነገሩን በመሆኑ የእኛ ድክመት እንጂ የነርሱ ጥንካሬ ፈጽሞ አይሆንምና እጥፊዎቹ እኛው ሲጠብ ዐማራ ሢሠፋ የሴሜቲክ ቁዋንቀዋ ተናጋሪ የሆነው ነን:: እናም “ሳይቃጠል በቅጠል” እንዲሉ የዚህን የኩሽቲክ ስብስብ ጥንስስ ከወዲሁ መላ ልንፈልግለት ይግባል::

የዐማራው ኅልውና መጠበቅ ለኢትዮጵያ እንድነት መጠበቅ ዋስትና ነው!